Skip to main content
Surveillance
Self-Defense

ከዊንዶውስ ላይ ውሂብዎን ደኅንነቱ በተጠበቀ መንገድ መሰረዝ

Last Reviewed: August 24, 2018

This page was translated from English. The English version may be more up-to-date.

የማውረጃ ሥፍራ:  https://www.bleachbit.org/download/windows

የኮምፒውተር ቅድመ ኹኔታ: ዊንዶው ኤክስፒ እና ከዚያ በላይ

በዚህ መመሪያ ጥቅም ላይ የዋለው ስሪት: ብሊችቢት 2.0

ፈቃድ: GPLv3

ደረጃ: ጀማሪ

የሚያስፈልገው ጊዜ: ከ10 ደቂቃዎች እስከ በርካታ ሠዓታት (ደኅንነቱ በተጠበቀ ኹኔታ እንዲሚሰረዘው ሰነድ ወይም ዲስክ መጠን)

ከታች ያሉት መመሪያዎች ውሂብ ተሽከርካሪ ድራይቮች ላይ ደኅንነቱ በተጠበቀ ሁኔታ እንዲወገድ ለማድረግ ብቻ ያገለግላሉ። እነዚህ መመሪያዎች የሚያገለግሉት ለቀድሞዎቹ ዲስክ ድራይቮች እንጂ በዘመናዊ ኮምፒውተሮች፣ የዩኤስቢ ቁልፎች/ የዩኤስቢ ተምብ ድራይቮች ወይም የኤስዲ ካርዶች/ፍላሽ ሚሞሪ ካርዶች ውስጥ በመደበኛነት የምናገኛቸው ሶሊድ ስቴት ድራይቮች(SSDs) አይደለም። በኤስኤስዲዎችን፣ የዩኤስቢ ፍላሽ ድራይቮች እና ኤስዲ ካርዶችን ደኅንነቱ በተጠበቀ መንገድ መሰረዝ በጣም ከባድ ነው! ይህ የሆነበት ምክንያት እነዚህ የድራይቭ አይነቶች ዊር ሌቭሊንግ የሚባል ዘዴን በመጠቀማቸው እና በውስጣው የያዙትን የመረጃ አሀዶች በዝቅተኛ ደረጃ ፍለጋ ስለማይሰጡ ነው። (ይህ ደኅንነቱ የተጠበቀ መሰረዝ ላይ እንዴት ችግር እንደሚያስከትል የበለጠ ለመረዳት እዚህ ማንበብ ይችላሉ።) ኤስኤስዲ ወይም ዩኤስቢ ፍላሽ ድራይቭ የሚጠቀሙ ከሆነ ከዚህ በታች ወዳለው ክፍልይዝለሉ።

ኮምፒውተርዎ ውስጥ የቆሻሻ መጣያ ቅርጫት ውስጥ ሰነድ ሲያስገቡ እና ቅርጫቱን ባዶ ሲያረጉበት ሰነዱ ሙሉ በሙሉ አለመጥፋቱን ያውቃሉ? ኮምፒውተሮች በመደበኝነት ሰነዶችን "አይሰረዙም"። አንድ ሰነድ ወደ ቆሻሻ ማጠራቀሚያ ሲያስገቡ ኮምፒውተርዎ ሰነዱን እንዳይታይ ያደርግና እና ፋይሉ የተጠራቀመበትን የዲስክ ክፍል ወደፊት ሌላ ሰነድ እንዲጻፍበት ክፍት ያደርገዋል:: ይህም አዲስ ውሂብ ከመጻፉ በፊት ሳምንታት፣ ወራት ወይም አመታት ሊወስድ ይችላል። ይህ እስኪሆን ድረስ ”የተሰረዘው“ ሰነድ ለተለመደው ተግባር እንዳይታይ ሆኖ በዲስኮዎት ላይ ይቆያል። እናም በትንሽ ድካም እና በትክክለኛ መሳሪያ (እንደ “አንዲሊት” ሶፍትዌር ወይም ፎርንሲክ ያሉ ዘዴዎች) “የተሰረዘውን” ፋይል መልሶ ማውጣት ይችላሉ።

ሰነድን ለዘላለም ለመሰረዝ ምርጡ መንገድ ወዲያውኑ በሌላ ነገር መተካቱን ማረጋገጥ ነው። ይህም መጀመሪያ ተጽፎ የነበረውን ሰነድ መልሶ ማውጣትን አዳጋች ያደርገዋል። ስርአተ ክወናዎ ለእርስዎ ይህንን ማድረግ የሚችል ሶፍትዌር ሊኖረው ይችላል። ይህ ሶፍትዌር በኮምፒውተርዎ ዲስክ ላይ ያለውን “ባዶ” ቦታ በሌሎች ትርጉም አልባ በሆኑ ውሂቦች ይተካል፤ በዚህም የተነሳ የተሰረዘው ውሂብ ሚስጥራዊነት ይጠብቃል።

በዊንዶውስ ብሊችቢት የተባለ ክፍት ምንጭ በዊንዶውስ እና ሊኒክስ የሚያገለግል ደኅንነቱ የተጠበቀ የስረዛ መሣሪያን እንዲጠቀሙ እንመክራለን። ብሊችቢት በቀላሉ እና በፍጥነት የተወሰኑ ሰነዶችን ደኅንነቱ በተጠበቀ መንገድ ለመሠረዝ ወይም በተወሰነ ጊዜ የሚደረግ የስረዛ መርሐግብርን ለመተግበር መጠቀም ይቻላል። የተበጀ የስረዛ ትዕዛዝም መጻፍ ይቻላል፡፡ ተጨማሪ መረጃዎችን በሰነዶች ውስጥ ያገኛሉ።

ብሊችቢት መጫን anchor link

በውንዶውስ መጫኛውን ከብሊችቢት ማውረጃ ገጽ ማግኘት ይችላሉ።

BleachBit installer.exe ትይይዝ ላይ ጠቅ ያድረጉ። ወደ ማውረጃ ገጹ ይወስድዎታል።

አብዛኞቹ የድር ማሰሻዎች ይህንን ሰነድ ማውረድ እንደሚፈልጉ ማረጋገጫ ይጠይቅዎታል። ማይክሮሶፍት 40ኛው ስሪት በድር መዳሰሻው ገጽ የታችኛው ክፍል ላይ ሰማያዊ ክፈፍ ያለው አሞሌ ያሳያል።

ለማንኛውም የድረ ገጽ ማሰሻ እጅግ በጣም ተመራጭ የሚሆነው ያወረዱትን ሰነድ ወደሚቀጥለው እንቅስቃሴ ከመግባትዎ በፊት ማስቀመጥ ነው። ስለዚህ “Save” የሚለው አዝራር ላይ ጠቅ ያድርጉ። በነባሪነት አብዛኞቹ የድር ማሰሻዎች የወረደውን ሰነድ በማውረጃ ማህደር ውስጥ ያስቀምጣሉ።

የዊንዶውስ ኤክስፕሎረር መስኮትን ክፍት ያድርጉ እና BleachBit-2.0-setup የሚለው ፋይል ላይ ሁለቴ ጠቅ ያድርጉ። በመቀጠልም ይህ ፕሮግራም እንዲጫን እንደሚፈቅዱ ይጠየቃሉ። ከዚያም “Yes” የሚለውን አዝራራ ጠቅ ያድርጉ።

አዲስ መስኮት ይከፈትና የመጫኛ ቋንቋን እንዲመርጡ ይጠይቅዎታል። የሚፈልጉትን ቋንቋ ይምረጡ እና “OK” የሚለውን አዝራር ጠቅ ያድርጉ።

የሚቀጥለው መስኮት GNU General Public License ያሳይዎታል። “I Agree” የሚለውን ይጫኑ።

በሚቀጥለው መስኮት ብሊችቢት አንዳንድ የማስተካከያ ምርጫዎችን ያሳያል። ምርጫዎቹን እንዳሉ መተው ይችላሉ። ከዴስክቶፕ ምርጫ ላይ የራይት ምልክቱን እንዲያጠፉ እንመክራለን። Next የሚለውን አዝራር ጠቅ ያድርጉ።

አሁን ብሊችቢት መጫን እንደሚፈልጉ እና እንደማይፈልጉ ለማረጋገጥ በድጋሚ ይጠይቅዎታል። Install የሚለውን አዝራር ጠቅ ያድርጉ።

በመጨረሻም የብሊችቢት መጫኛ ፕሮግራሙን መጫን እንደጨረሰ የሚናገር መስኮት ያሳይዎታል። Next የሚለውን አዝራር ጠቅ ያድርጉ።

የመጫኛው የመጨረሻ መስኮት ብሊችቢትን ማስኬድ እንደሚፈልጉ እና እንደማይፈልጉ ይጠይቅዎታል። Run ብሊችቢት ምርጫ ላይ ያለውን የራይት ምልክት ያጥፉት። Finish የሚለውን አዝራር ጠቅ ያድርጉ።

ብሊችቢትን መጠቀም anchor link

ወደ Start ምናሌ ይሂዱና የዊንዶውስ አዶን ጠቅ ያድርጉ እና ከምናሌው ብሊችቢትን ይምረጡ።

ትንሽ መስኮት ይከፈት እና ብሊችቢትን መክፈት እንደሚፈልጉ ያረጋግጣል። “Yes” የሚለውን አዝራር ጠቅ ያድርጉ።

ዋናው የብሊችቢት መስኮት ይከፈታል። ብሊችቢት የተለያዩ በተለምዶ የተጫኑ መተግበሪያዎችን ይመረምር እና ለእያንዳንዱ መተግበሪያ የተለየ ምርጫን ያሳያል።

ቅድመ-ቅምጥን መጠቀም anchor link

ብሊችቢት የኢንተርኔት ኤክስፕሎረር ቅድመ-ቅምጥን በመጠቀም ኢንተርኔት ኤክስፕሎረር ጥሎ የሚያልፈውን ምልክቶች መጥረግ ይችላል። ከኢንተርኔት ኤክስፕሎረር ጎን ያለውን ሳጥን ይምረጡ። ለኩኪዎች፣ ፎርም ሂስትሪ፣ ሂስትሪ፣ እና ቴምፖረሪ ፋይልስ የሚሉት ምርጫዎች የተመደቡ ሳጥኖች መመረጣቸውን ያስተውሉ። እንደአስፈላጊነቱ እነዚህን ሳጥኖች አለማመልከት ይችላሉ። Clean የሚለውን አዝራር ጠቅ ያድርጉ።

አሁን ብሊችቢት አንዳንድ ሰነዶችን ያጸዳ እና ሂደቱን ያሳይዎታል::

ማህደርን ደኅንነቱ በተጠበቀ መንገድ መሰረዝ anchor link

ፋይል ምናሌ ላይ ጠቅ ያድርጉ እና ሽሬድ ፎልደርስን ይምረጡ።

ትንሽ መስኮት ይከፈታል። መደምሰስ የሚፈልጉትን ማህደር ይምረጡ።

ብሊችቢት የመረጧቸውን ሰነዶች በቋሚነት መሰረዝ እንደሚፈልጉ እና እንደማይፈልጉ ለማረጋገጥ ይጠይቅዎታል። Delete የሚለውን አዝራር ጠቅ ያድርጉ።

አሁን ብሊችቢት የሰረዟቸውን ሰነዶች ያሳይዎታል። ብሊችቢት በማህደሩ ውስጥ ያሉ እያንዳንዱን ሰነድ በመቀጠልም ማህደሩን ደኅንነቱ በተጠበቀ መንገድ እንደሚሰርዝ ይወቁ።

ሰነድን ደኅንነቱ በተጠበቀ መንገድ መሰረዝ anchor link

ፋይል ምናሌውን ጠቅ ያድርጉ እና ሽሬድ ፋይልስ የሚለውን ይምረጡ።

ሰነድ የመምረጫው መስኮት ይከፈታል። መደምሰስ የሚፈልጓቸውን ሰነዶች ይምረጡ።

ብሊችቢት የመረጧቸውን ፋይሎች በቋሚነት መሰረዝ እንደሚፈልጉ እና እንደማይፈልጉ ለማረጋገጥ ይጠይቅዎታል። Delete የሚለውን አዝራር ጠቅ ያድርጉ።

ብሊችቢት ብዙ ሌሎች አገልግሎቶች አሉት። ምናልባትም “ዋይፕ ፍሪ እስፔስ” በጣም ጠቃሚው አገልግሎቱ ነው። ይህም ቀድመው የሰረዟቸው ፋይሎች ማንኛውንም አይነት ምልክት ለማስወገድ ይሞክራል። አብዛኛውን ጊዜ ሊኒክስ የተሰረዘውን ውሂብ ሙሉ ወይም የተወሰነ ክፍሉን በሃርድ ድራይቩ ቀሪ ባዶ ቦታ ላይ ያስቀምጣል። “ዋይፕ ፍሪ እስፔስ” እነዚህ ባዶ ናቸው ተብለው የሚገመቱ የሀርድ ድራይቩ ክፍሎችን በዘፈቀደ በተሰራ ውሂብ ይተካዋል። ድራይቭዎ ባለው ትርፍ ባዶ ቦታ መሰረት ባዶ ቦታውን መጥረግ ብዙ ጊዜን ሊወስድ ይችላል።

ስለ ደኅንነቱ የተጠበቀ መሰረዣ መሳሪያዎች ገደቦች ማስጠንቀቂያ anchor link

ከላይ ያለው ምክር በሚጠቀሙበት ኮምፒዩተር ዲስክ ላይ ሰነዶችን ብቻ ይሰርዛል። ከላይ ያሉት ማናቸውም መሳሪያዎች በኮምፒተርዎ፣ በሌላ ዲስክ ወይም የዩኤስቢ ድራይቭ፣ "Time Machine"፣ በኢሜይል ሰርቨር፣ በደመና ውስጥ ወይም ወደ እውቅያዎችዎ የተላኩትን የመጠባበቂያ ቅጂዎችን አይሰርዙም። አንድን ፋይል በአስተማማኝ ሁኔታ ለመሰረዝ፣ ያጠራቀመበት ወይም የተላከበትን ሁሉም ቦታ ቅጂዎችን ማጥፋት አለብን። በተጨማሪም አንድ ፋይል በደመናው ውስጥ ከተከማቸ (ለምሳሌ:- በ ድሮፕቦክስ ወይም በሌላ ሰነድ ማጋሪያ አገልግሎት አማካኝነት) ለዘላለም የሚጠፋበት መንገድ የለም።

እንደአለመታደል ሆኖ ሌሎች ደኅንነቱ የተጠበቀ መሰረዣ መሳሪያዎች ሌሎች ገደቦች አሉባቸው። ከላይ የተሰጠውን ምክር ቢከተሉ እና ሁሉንም የሰነድ ቅጂዎችን ቢደመስሱ እንኳ የተደመሰሱ ሰነዶች ጥቂት ዱካ በኮምፒውተራችን ላይ ሊቆዩ የሚችሉበት እድል አለ። ሰነዶቹ በትክክል ስላልተደመሰሱ ሳይሆን የተወሰኑ የስርዓተ ክወና ክፍሎች ወይም ሌሎች መተግበሪያዎች ሆን ተብሎ የተመዘገቡበትን መዝገብ ይይዛሉ።

ይህ ሊመጣ የሚቻልባቸው በርካታ መንገዶች አሉ። ነገር ግን ሁለት ምሳሌዎችን ማንሳት ሊሆን የሚችልበት ዕድሎች እንዳሉ ለማሳየት በቂ ናቸው። በዊንዶውስ ወይም ማክኦኤስ፣ ማይክሮሶፍት ኦፊስ በ"የቅርብ ጊዜ ሰነዶች" ምናሌ ውስጥ ሰነዱ ቢሰረዝም(አንዳንድ ጊዜ ኦፊስ የይዘት ፋይሎችን የያዘ ጊዜያዊ ቅጂም ሊያስቀምጥ ይችላል) የሰነድ ስም ሊያኖሩ ይችላሉ። ሊብሬኦፊስ እንደ ማይክሮሶፍት ኦፊስ ብዙ መዝገቦችን ሊይዝ ይችላል። እናም ምንም እንኳን ፋይሉ በአስተማማኝ ሁኔታ ቢሰረዝም የተጠቃሚው ዝርዝር የሰነድ ታሪክ የሰነዱን ስም ያካተተ ትዕዛዞችን የያዘ ሊሆን ይችላል። በተግባር ግን እንደዚህ አይነት ባህሪ ያላቸው በደርዘን የሚቆጠሩ ፕሮግራሞች ሊኖሩ ይችላሉ።

ለዚህ ችግር እንዴት ምላሽ መስጠት እንደሚቻል ማወቅ በጣም አስቸጋሪ ነው። አንድ ሰነድ ደኅንነቱ በተጠበቀ ሁኔታ ከተሰረዘ በኋላ እንኳን ስሙ ለተወሰነ ጊዜ በኮምፒውተሩ ላይ ይኖራል። ስሙ በሙሉ ጠፍቶ እንደሆነ 100% እርግጠኛ ለመሆን ብቻ ዲስኩን በሙሉ እንደገና መጻፍ ብቸኛው መንገድ ነው። አንዳንዶቻችሁ "መረጃው የትኛውም ቅጂ ወደ የትኛውም ቦታ መኖሩን ለማየት ዲስኩ ላይ ጥሬ ውሂብ መፈለግ እችላለኹ?" ብለው ይጠይቁ ይሆናል። መልሱ አዎን እና አይደለም የሚል ነው። ዲስኩን መበርበር ውሂቡ በዲስክ ውስጥ የሚገኝ እንደሆነ ይነግርዎ ይሆናል። ነገር ግን አንዳንድ ፕሮግራሞች የተጨመቁ ወይም በሌላ መንገድ የተጣቀሱ ማጣቀሻዎች ካሉ አይነግርዎትም። በተጨማሪም ፍለጋው ራሱ አሻራ እንዳይተው ይጠንቀቁ! የፋይሉ ይዘቶች ሊገኙ የሚችሉበት ዕድል ዝቅተኛ ቢሆንም ግን የማይሆን አይደለም። ሙሉውን ዲስክ መገልበጥ እና አዲስ ስርዓተ ክወና መጫን ሰነዱ እንደ ተሰረዘ 100% እርግጠኛ ለመሆን ብቸኛው መንገድ ነው።

ያረጀ ሃርድዌር ማስወገድ ሲያስፈልግ የሚደረግ ደኅንነቱ የተጠበቀ ስረዛ anchor link

አንድ የሃርድዌርን መጣል ወይም በኢቤይ ላይ ለመሸጥ የሚፈልጉ ከሆነ ማንም ሰው የእርስዎን ውሂብ ማውጣት አለመቻሉን ማረጋገጥ ይፈልጋሉ። ጥናቶች እንደሚያሳዩት የኮምፒውተር ባለቤቶች ብዙውን ጊዜ እንዲህ ማድረግ አይሳካላቸውም። ሃርድ ድራይቮች ብዙ ጊዜ ከፍተኛ ሚስጥራዊ የሆኑ መረጃዎችን እንደያዙ ነው እንደገና የሚሸጡት። ስለዚህ ኮምፒውተር ከመሸጥ ወይም እንደገና ጥቅም ላይ ከመዋልዎ በፊት በመጀመሪያ, በውስጡ ያለውን የመረጃ ማጠራቀሚያ በማይረባ ነገር መተካትዎን ያረጋግጡ። ምንም እንኳን ወዲያውኑ ባያስወግዱት ህይወቱ ያበቃ ኮምፒውተር ካለዎትና ከአሁን በኋላ ጥቅም ላይ የማይውል ከሆነ አንድ ጥግ ላይ ወይም ቁም ሳጥን ውስጥ ከማስቀመጥዎ በፊት ሃርድ ድራይቩን ማጽዳት የበለጠ አስተማማኝ ይሆናል። ‘ድሪክስ ቡት ነደ ኑክ’ ለዚህ ዓላማ የተሰራ መሣሪያ ሲሆን እንዴት መጠቀም እንደሚቻል የሚያሳዩ በርካታ መልመጃዎች ( ይህንን ጨምሮ) በመላው ድር ይገኛሉ።

አንዳንድ ሙሉ ዲስክ ምስጠራ ሶፍትዌሮች የመደበኛ ቁልፉን የማጥፋት ችሎታ አላቸው። በመሆኑም የተመሰጠሩ የሃርድ ድራይቭ ይዘቶችን መገልበጥ ፈጽሞ አይቻልም። ቁልፉ ትንሽ መጠን ያለው መረጃ በመሆኑ እና በፍጥነት ሊጠፋ በመቻሉ እንደ ድሪክስ ቡት ነደ ኑክ ካሉ ሶፍትዌሮች ጋር ለትልቅ ድራይቮች በጣም ብዙ ጊዜ ሊወስድ የሚችለውን እንደገና ለመጻፍ በጣም ፈጣን አማራጭ ነው። ሆኖም ግን ይህ አማራጭ ተገቢ የሚሆነው ሃርድ ድራይቮ ሁልጊዜ የሚመሰጠር ከሆነ ነው። ሙሉ ዲስክ ምስጠራን ቀድመው የማይጠቀሙ ከሆነ ከማስወገድዎ በፊት ሙሉውን ዲስክን እንደገና መጻፍ ያስፈልግዎታል።

ሲዲ ወይም ዲቪዲ-ሮምስ ማስወገድ anchor link

ሲዲ ወይም ዲቪዲ-ሮም ወደማስወገድ ጋር ስንመጣ ወረቀት ሲያስወግዱ እንደሚያደርጉ ተመሳሳይ ነገር ማድረግ አለብዎ። ብዙ ገንዘብ የማያባክኑ ማስወገጃዎች አሉ። ምንም ስሱ መረጃዎች አለመያዛቸውን ፍጹም እርግጠኛ ካልሆኑ በስተቀር ሲዲ ወይም ዲቪዲ-ሮምን ወደ ቆሻሻ ቅርጫት አይወርውሩ።

ሶሊድ ስቴት ዲስኮችን(SSDs)፣ ዩኤስቢ ፍላሽ ድራይቮችን እና ኤስዲ ካርዶችን ደኅንነቱ በተጠበቀ መንገድ መሰረዝ anchor link

እንደ አለመታደል ሆኖ በአሰራር ስልታቸው ምክንያት ሶሊድ ስቴት ዲስኮችን(SSDs)፣ ዩኤስቢ ፍላሽ ድራይቮችን እና ኤስዲ ካርዶች ውስጥ ያሉ ሰነዶችን ወይም ባዶ ቦታዎችን ለመሰረዝ አይቻልም ለማለት ቢከበድ እንኳን አስቸጋሪ ነው። በዚህ ምክንያት ራስዎን ከመጠበቅ አንፃር እጅግ የተሻለው አማራጭ ምስጠራ ነው። እንዲህ ካደረጉ በኋላ ሰነዱን በዲስክ ውስጥ ማንኛውም ሰው ቢያገኘው እንኳን የሚመለከተው እንደ የማይረባ ነገር ነው፡፡ እናም ምስጠራውን እንዲፈቱ ሊያስገድድዎት አይችልም። በአሁን ሰዓት ከኤስኤስዲ ላይ መረጃዎን የሚያስወግድ ጥሩ የሚባል አጠቃላይ ቀደም ተከተል ማቅረብ አንችልም። ለምን ውሂብ መሰረዝ በጣም ከባድ እንደሆነ ማወቅ ከፈለጉ ንባብዎን ይቀጥሉ።

ቀደም ብለን እንደጠቀስነው ኤስኤስዲ እና የዩኤስቢ ፍላሽ ድራይቮች ዊር ሌቭሊንግ የተባለ ስልት ይጠቀማሉ። ዊር ሌቭሊንግ በከፍተኛ ደረጃ የሚሰራው እንደሚከተለው ነው። በመጽሐፍ ውስጥ እንዳሉ ገጾች በዲስክ ውስጥ ያለው በእያንዳንዱ ቦታ በብሎኮች የተከፈለ ነው። አንድ ሰነድ በዲስክ ላይ ሲጻፍ የተወሰነ ብሎክ ወይም ብሎኮች(ገጾች) ይይዛል። ሰነዱን ለመተካት ከፈለጉ ማድረግ ያለብዎት ለዲስኩ በብሎኮች ላይ እንደገና እንዲጽፍ መንገር ነው። ነገር ግን በኤስኤስዲ እና የዩኤስቢ ፍላሽ ድራይቮች በመሰረዝ እና እንደገና መጻፍ ብሎኩን ከጥቅም ውጭ ሊያደርገው ይችላል። ማገልገል የማይችል እስኪሆን ድረስ እያንዳንዱ ብሎክ በማጥፋት እና እንደገና መጻፍ ሊያገለግል የሚችልበት መጠን የተገደበ ነው።(ልክ በአንድ የወረቀት ገጽ ላይ ደጋግመው በእርሳስ እየጻፉ ቢያጠፉ ወረቀቱ እንደሚቀደድ ወይም ከጥቅም ውጭ እንደሚሆነው ማለት ነው።) ይህን ለመመከት ኤስኤስዲ እና የዩኤስቢ ፍላሽ ድራይቮች እያንዳንዱ ብሎክ ላይ የሚጻፈው እና የሚጠፋው ብዛት ተመሳሳይ መሆኑን ለማረጋገጥ ይሞክራሉ፤ በዚህም ድራይቩ በተቻለ መጠን ለረዥም ጊዜ ይቆያል። ይህ ሂደት ነው ዊር ሌቭሊንግ የሚባለው። እንደ የጎንዮሽ ጉዳት አንዳንድ ጊዜ ሰነዱ በመጀመሪያ የተቀመጠበትን ብሎክ በማጥፋት እና እንደገና በመጻፍ ፋንታ ያንን ብሎክ በመተው ወይም የማይሰራ የሚል ምልክት በመተው የተቄረውን ሰነድ በተለየ ብሎክ ያስቀምጣል። ይህ በመጽሐፉ ውስጥ ገጹን ሳይለውጥ የተሻሻለውን ፋይል በመጻፍ እና በሌላ የመዝገበ-ቃሉ ማውጫ ላይ ወደ አዲሱ ገፅ እንደገና መጻፍ ማለት ነው። ይህ ሁሉ የሚሆነው በዲስክ ኤሌክትሮኒክስ ውስጥ በጣም ዝቅተኛ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ነው የሚከሰተው። ስለዚህ ስርዓተ ክወናው ምን እንደፈጠረ እንኳን አያውቅም። ይሄ ማለት አንድ ሰነድ ላይ ደርቦ ለመጻፍ ቢሞክር እንኳ ድራይቮ በትክክል ደርቦ እንደገና ለመጻፉ ምንም ዋስትና የለም። ለዚህም ነው የኤስኤስዲዎችን ደኅንነቱ በተጠበቀ መንገድ መሰረዝ ይህን ያህል ከባድ የሆነው።